19 June 2013
ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ በሀገሪቱ 4 ትሪሊየን ሜትሪክ ኩብ የተፈጥሮ ጋዝ መኖሩ ገለፀ
አዲስ አበባ ነሀሴ 12/2004/ዋኢማ/ - በኦጋዴን ቤዚን በሚገኘው የካሉብና ኢላላ አካባቢ አራት ትሪሊየን ሜትሪክ ኩብ የተፈጥሮ ጋዝ ክምችት እንዳለ መረጋገጡን የማዕድን ሚኒስቴር አስታወቀ።
በሚኒስቴሩ የህዝብ ግንኙነት ኮሙኒኬሽን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ባጫ ፋጂ ለዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል እንደገለፁት፤ በኦጋዴን አካባቢ ከተገኘው በተጨማሪም ገናሌ አካባቢ 0 ነጥብ 7 ትሪሊየን ወይም 700 ቢሊየን ሜትሪክ ኩብ የተፈጥሮ ጋዝ ክምችት እንዳለ በጥናት ተረጋግጧል።
በመቀሌ እና መተማ ቤዚኖች ያለው የመሬትና የድንጋይ አፈጣጠርም በአካባቢዎቹ ነዳጅ ሊኖር እንደሚችል ጠቋሚ ነው ብለዋል።
እንደ አቶ ባጫ ገለፃ በጋምቤላ ቤዚንም ነዳጅ ሊኖር እንደሚችል ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የታዩ ተደጋጋሚ ፍንጮች አመልክተዋል።
የአባይና ስምጥ ሸለቆ ቤዚኖችም ሌሎች ነዳጅ ይኖርባቸዋል ተብለው የተገመቱ አካባቢዎች ናቸው ብለዋል።
በእነዚህ አካባቢዎች በአጠቃላይ ዘጠኝ የተለያዩ ኩባንያዎች የነዳጅ ፍለጋ ስራ እያካሄዱ እንደሚገኙ ነው ዳይሬክተሩ፤ በአጠቃላይ 2 ነጥብ 4 ቢሊየን የአሜሪካ ዶላር በማስመዝገብ ወደ ስራ እንደገቡ ገልፀዋል።
| < Prev | Next > |
|---|


