በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የአዲስ አበባ ከተማ የመንገድ ሽፋን 13 ነጥብ 7 በመቶ ደርሷል

  • PDF

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 28/2004 (ዋኢማ) - የአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን በተጠናቀቀው የ2004 በጀት ዓመት የመዲናዋ የመንገድ ሽፋን 13 ነጥብ 7 በመቶ መድረሱን አስታወቀ።

የባለስልጣኑ ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጅነር ፍቃዱ ኃይሌ ዛሬ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ላይ እንዳስታወቁት የከተማዋን የመንገድ ሽፋን ለማሳደግ ሰፊ ሥራ ተከናውኗል።

በዚህም 12 ነጥብ 9 በመቶ የነበረው የአዲስ አበባ ከተማ የመንገድ ሽፋን ወደ 13 ነጥብ 7 በመቶ ሲያድግ የመንገድ መረቡም ከነበረበት 3 ሺህ 512 ኪሎ ሜትር ወደ 3 ሺህ 731 ኪሎ ሜትር ማደጉን ተናግረዋል።

በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች የውስጥ ለውስጥ መንገዶችና የእግረኛ መንገድና 207 ኪሎ ሜትር ኮብል ስቶን የማንጠፍ ሥራ መከናወኑን ገልጸዋል።

በሌላ በኩል በበጀት ዓመቱ 66 ነጥብ 08 ኪሎ ሜትር አዲስ የአስፋልት መንገድ ለመስራት ታቅዶ 46 ኪሎ ሜትር ማከናወን የተቻለ ሲሆን ይህም የዕቅዱን 69 በመቶ ያህል ነው ብለዋል፡፡

ባለስልጣኑ ባከናወናቸው የአዲስ መንገድ ፣ የድልድይ፣ የአስፋልት ጥገና፣ የጠጠር መንገድ፣ የፍሳሽ ማስወገጃ፣ የእግረኛ መንገድ ግንባታና ጥገና እንዲሁም የትራፊክ ኦፕሬሽን ሥራዎች ላይ ከ3 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል ማስገኘቱን አመልክተዋል፡፡

የሥራ ተቋራጮች አፈፃፃም ከተጠበቀው በታች መሆን፣ የግንባታ መሳሪያዎች እጥረት፣ በመንገድ መስመር ላይ የሚገኙ የውኃና የመብራት መስመሮች እንዲሁም ቤቶች በተፈለገው ፍጥነት ያለመነሳት ካጋጠሙ ችግሮች ተጠቃሽ ናቸው ማለታቸውን የዘገበው ኢዜአ ነው፡፡

  • Facebook Page: 204028600784
  • FeedBurner: waltainfo/LdbW
  • Flickr: waltainformationcenter
  • Twitter: walta_info
  • YouTube: waltainformation
 304 guests