ጣሊያን በኢኮኖሚ ዘርፍ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ግንኙነት ማጠናከር እንደምትፈልግ አስታወቀች

  • PDF

አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 26 2004/ዋኢማ/ - ጣሊያን በኢኮኖሚ ዘርፍ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ግንኙነት ይበልጥ ማጠናከር እንደምትፈልግ የሀገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አስታወቁ፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ጋር ተወያይተዋል፡፡

በኢትዮጵያ የሥራ ጉብኝት በማድረግ ላይ የሚገኙት የጣሊያን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጁሊዮ ቴርዚ ደሳንት ከጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ጋር በሁለቱ አገራት ግንኙነትና በአፍሪካ በተለይም በምስራቅ አፍሪካ ጉዳዮች ላይ ተወያይተዋል።

ጣሊያንና ኢትዮጵያ በፖለቲካውና በሌሎች ጉዳዮች ዙሪያ መልካም ግንኙነት አላቸው ያሉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በኢኮኖሚው መስክም ጣሊያን ከኢትዮጵያ ጋር  በጋራ ለመስራት ፍላጎት እንዳላት ተናግረዋል።

በተለይም ኢትዮጵያ የነደፈችውን የአምስት ዓመቱን የእድገትና ትራንስፎርሜሸን እቅድ ለማሳካት አገራቸው በኢንዱስትሪው ዘርፍ የነቃ ተሳትፎ ለማድረግ ፍላጎት እንዳላት አረጋግጠዋል።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ጋር በነበራቸው ቆይታ በአካባቢው የፀጥታ ጉዳይ ላይም ተወያይተዋል፡፡

በሁለቱ ሱዳኖች መካከል ለተፈጠረው አለመግባባት እልባት ለመስጠት ኢትዮጵያ በኢጋድ በኩል ጣሊያን ደግሞ በአውሮፓ ህብረት በኩል የበኩላቸውን ኃላፊነት ለመወጣት እንደሚሰሩም  በውይይቱ ወቅት ተናግረዋል፡፡

በሶማሊያ የተጀመረውን ሰላምና መረጋጋት ለማስቀጠል በሚቻልበትና የኤርትራን ፀብ አጫሪነት ድርጊት ለማስቆም በሚቻልበት ሁኔታ ላይም መክረዋል፡፡

ኢትዮጵያን እየጎበኙ የሚገኙት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጁሊዮ ቴርዚ ደሳንት   ከምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ጋር በሁለትዮሽና አለም አቀፍ ጉዳዮች ዙሪያ መክረዋል፡፡

የኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ እንዳሉት ምክክሩ በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተው የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት እንዲጎለብት ከማስቻሉም በላይ የንግድና ኢንቨስትመንት ትስስሩን ያጠናክራል፡፡

በምስራቅ አፍሪካ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን የሚደረገውን ጥረትም ያግዛል ብለዋል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ ፡፡

እንደ ሚኒስትሩ ገለጻ በክፍለ አህጉሩ ያሉ አለመግባባቶች እንዲፈቱ የጣሊያንና የኢትዮጵያ መንግስት የጋራ ጥረት ማድረግ አለባቸው፡፡

ሚኒስትሩ በኢትዮጵያ ባለው ሰፊ ዕድል የጣሊያን ባለሃብቶች በግብርና፣ በኢንዱስትሪ፣ በሃይድሮ ኤሌክትሪክ ኃይል ያላቸውን ተሳትፎ እንዲያሳድጉም ጥሪ አቅርበዋል፡፡

የጣሊያኑ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጆሲ ቴርዚ ደሳንት በበኩላቸው መንግስታቸው በኢትዮጵያ እየተካሄደ ያለውን ልማትና ሀገሪቱ በአለም አቀፍ ሰላም ማስከበር ዙሪያ እያበረከተችው ያለውን ሚና አድንቀዋል፡፡

በሽብርተኝነት ዙሪያ ያላትን አቋም በማድነቅ ኢትዮጵያ በሶማሊያ፣ በሱዳንና በደቡብ ሱዳን ሰላም እንዲሰፍን ከኢጋድና ከሌሎች ሀገራት ጋር በመሆን የምታደርገውን ጥረት እንደሚደግፉም ተናግረዋል፡፡

የጣሊያኑ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢትዮጵያን እንዲጎበኙ የተጋበዙት ባለፈው መጋቢት በሮም በተካሄደው የኢትዮ-ጣሊያን የንግድ ፎረም የጋራ መድረክ ላይ እንደነበር የዘገበው ኢሬቴድ ነው ፡፡

  • Facebook Page: 204028600784
  • FeedBurner: waltainfo/LdbW
  • Flickr: waltainformationcenter
  • Twitter: walta_info
  • YouTube: waltainformation
 414 guests