አዲስ አበባ ግንቦት 4/2000/ዋኢማ/ በኦሮሚያ ክልል የዋጋ ንረትን የሚያባብሱ ህገ ወጥ የንግድ እንቅስቃሴዎችን የሚቆጣጠር ኮሚቴ እስከ ወረዳ ድረስ ተቋቁሞ እየሰራ መሆኑን የክልሉ ንግድ፣ ኢንዱስትሪና ትራንስፖርት ቢሮ አስታወቀ። ደላላዎችና የንግድ ፍቃድ ሳይኖራቸው የግብርና ውጤቶችን ገዝተው የሚያከማቹ ግለሰቦች ችግሩን የሚያባብሱ አካላት እንደሆኑ ተለይተዋል።
የቢሮው ኃላፊ አቶ ቱጃር ቃሲም ለዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል እንዳስታወቁት፤ በአገሪቷ በተመዘገበው የኢኮኖሚ እድገት ሳቢያ በተፈጠረው የአቅርቦትና የመግዛት ፍላጎት አለመጣጣምና የዓለም የነዳጅ ዋጋ መጨመርን ተከትሎ የተከሰተውን የሸቀጦች ዋጋ ንረት የሚያባብሱ ህገ ወጥ የንግድ እንቅስቃሴዎችን ለመቆጣጠር የተቋቋመው ኮሚቴ አበረታች ተግባራትን በማከናወን ላይ ይገኛል።
ከመጋቢት ወር ጀምሮ በክልል፣ በዞን፣ በወረዳና ዋና ዋና ከተሞች የተቋቋመው ኮሚቴ በየደረጃው የችግሩን መንስኤዎች በዝርዝር በማጥናት ህብረተሰቡንና ህጋዊ ነጋዴዎችን የመፍትሔ አካል ለማድረግ የሚያስችሉ ውይይቶች ማካሄዳቸውን ኃላፊው ገልጸዋል።
ከፀጥታና የፍትህ አካላት፣ ከአስተዳደር፣ ከንግድ፣ ኢንዱስትሪና ትራንስፖርትና ሌሎች ከሚመለከታቸው አካላት የተውጣጡ አባላት ያሉት ይህው ኮሚቴ በብዛት ለፍጆታ በሚውሉ የግብርናና የኢንዱስትሪ ወጤቶች ላይ በማትኮር ከአምራቹ እስከ ተጠቃሚው ድረስ ያለውን የአቅርቦት ችግር በመለየት የመፍትሔ እርምጃዎች መውሰድ መጀመሩን አመልክተዋል።
በዚሁ መሰረት በምርት አቅርቦትና ተጠቃሚዎች መካከል እየገቡ የገበያ ሰንሰለቱን የሚያራዝሙና ጤናማ የንግድ እንቅስቃሴ እንዳይኖር የሚያደርጉ ደላላዎች በህብረተሰቡ ጥቆማ ከገበያው መሐል እንዲወጡ እየተደረገ መሆኑን አቶ ቱጃር ገልጸዋል።
እንዲሁም አጋጣሚውን ተጠቅመው ፍትሃዊ ያልሆነ ትርፍ ለማጋበስ ያለአግባብ የዋጋ ጭማሪ ለማያደርጉት ነጋዴዎች ትምህርትና ማስጠንቀቂያ እየተሰጠ ከድርጊታቸው የማይታቀቡትን የንግድ ድርጅታቸውን ከማሸግ ጀምሮ ወደ ህግ እስከ ማቅረብ የሚደርስ እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን ተናግረዋል።
የንግድ ፍቃድ ሳይኖራቸው በየገጠሩ ገበያን በመውረር የግብርና ውጤቶችን ገዝተው የሚያከማቹና እጥረት ሲፈጠር በውድ ዋጋ አውጥተው የሚሸጡ ግለሰቦችም ችግሩን የሚያባብሱ ሆነው በመገኘታቸው ወጥ በሆነ መንገድ ለመቆጣጠር የሚያስችል መመሪያ እየተዘጋጀ እንደሚገኝ ኃላፊው አስታውቀዋል።
የዋጋ ንረቱ በአስተማማኝ ሁኔታ እስኪረጋጋ ድረስ ኮሚቴው በቀበሌና በአነስተኛ ከተሞች ጭምር እንዲዋቀርና ተጠናክሮ ስራውን እንዲቀጥል ቢሮው ክትትልና ድጋፍ የሚያደርግ መሆኑንም መናገራቸውን ዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል ዘግቧል ።