አዲስ አበባ ግንቦት 4/2000/ዋኢማ/ የኤርትራ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች በአንድነት ለመስራት መወሰናቸው ኤርትራትራዊያን የጓጓለትን ሰላም፣ ዴሞክራሲና ፍትህ ለማጎናጸፍ የሚያስችል እርምጃ እንደሆነ ተገለጸ። ዓለም አቀፉ ማህረሰብ በአምባገነናዊው ስርዓት ተማረው ከአገራቸው ለተሰደዱ የኤርትራ ስደተኞች የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንዲቀጥልም ጉባኤው ጠይቋል።
አስራ ሦስት የኤርትራ የፖለቲካ ፓርቲዎች አምባገነኑን የኢሳያስ አገዛዝ ለመገርሰስ የሚያስችላቸውን ህብረት የመሰረቱበትን ጉባኤ ሲያጠቃልሉ ያወጡት የአቋም መግለጫ እንደሚያስረዳው፤ ፓርቲዎቹ የፈጠሩት አንድነት የኤርትራ ህዝብ አምባገነኑን ስርዓት ለመጣል የሚያደርገውን ትግል ውጤታማነት ያፋጥነዋል።
ለተከታታይ ሰባት ቀናት በአዲስ አበባ የተካሄደው ጉባኤ ፓርቲዎች ከመቼውም ጊዜ በበለጠ በመግባባትና በመከባበር ያካሄዱት መሆኑን የገለጸው መግለጫው፤ በድህነትና በጦርነት የተሰቃየውን የኤርትራ ህዝብ የዴሞክራሲ፣ የሰላምና የልማት ተጠቃሚ ለማድረግ ትግሉን በአንድነት ለማፋፋም የተስማሙበት መሆኑን አመልክቷል።
በጉባኤው አዲሱ የኤርትራ ዴሞክራሲያዊ ህብረት የሚመራበት ቻርተርና ህገ ደንብ በተሳታፊዎች በሙሉ ድምጽ መጽደቁን ጠቁሞ፤ ሃያ ሦስት አባላትን የህብረቱ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ሆነው እንዲያገለግሉ የመረጠ ሲሆን አገራዊ ዴሞክራሲያዊ ለውጥ ለማምጣት ትግሉ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቋል።
የጉባኤው ሊቀመንበር ዶክተር ሃብቴ ተስፋማሪያም ለጋዜጠኞች እንደገለጹት፤ ህብረቱ ኤርትራ ከሌሎች አገራት ጋር ያላትን ማንኛውንም ችግር በሰላማዊ አግባብ ለመፍታት ፍላጎት አለው።
ሶማሌያውያንም የራሳቸውን ችግር በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት የሚያደርጉትን ጥረት አጠናክረው መቀጠል እንደሚገባቸውና በጅቡቲ ሸምጋይነት እየተካሄደ ያለውን ድርድር ህብረቱ እንደሚደግፍ ገልጸው፤ ኤርትራውያን አምባገነኑን ስርዓት ለመጣል በሚያደርጉት ጥረት ድጋፍ እያደረጉ ላሉ መንግስታትና አካላት ምስጋና አቅርበዋል።
ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ድርጅቶችና የመንግስታቱ ድርጅት የኢሳያስ መንግስት በዜጎቹ ላይ እያደረሰ ያለውን ሰቆቃ በመከታተል እንዲያጋልጡ የጠየቁት ዶክተር ሀብቴ፤ በደረሰባቸው በደል ከአገር ለተሰደዱ ኤርትራውያንም ለጋሽ አገራትና ድርጅቶች እያደረጉት ያለውን ሰብዓዊ ድጋፍ አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጥሪ አቅርበዋል።
አምባገነኖችን ለመጣል እየተደረገ ያለው ትግል የመጨረሻ ደረጃ ላይ መድረሱን አመልክተው፤ በሰላምና በዴሞክራሲ እጦት እየተሰቃየ ያለው የኤርትራ ህዝብ የኢሳያስን መንግስት ለመገርሰስ ትግሉን ይበልጥ እንዲያቀጣጥል ጠይቀዋል።
በጉባኤው ላይ የኤርትራ የሃይማኖት መሪዎችና የሲቪክ ማህበራት ተወካዮች መሳተፋቸውን ዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል ዘግቧል።