የስልጤ ህዝብ በልማትና መልካም አስተዳደር ዘርፎች ተጠቃሚነቱ መረጋገጡ ተገለፀ

ሐዋሳ ግንቦት 1/2000/ዋኢማ/ በደቡብ ክልል የስልጤ ህዝብ በልማትና በመልካም አስተዳደር ዘርፎች ተጠቃሚነቱ እየተረጋገጠ መምጣቱን የዞኑ ዋና አስተዳደሪ ገለፁ።በዞኑ የሚሊኒየሙ የግል ድርጅቶች፣ባለሃብቶችና ነጋዴዎች እንዲሁም የወጣቶች ፌስቲቫል ትናንት በወራቤ ከተማ ተካሂዷል።

የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሳኒ ረዲ ፌስቲቫሉን በንግግር ሲከፍቱ እንዳሉት የስልጤ ህዝብ በዞን ደረጃ ከተቋቋመ ከ1993 ዓ.ም ወዲህ በትምህርት፣በጤና፣በመሠረተ ልማት፣በመልካም አስተዳደርና በተለያዩ የምጣኔ ሀብት እድገት ዘርፎች ተጠቃሚነቱ ተረጋግጧል።

በተለይ ቀደም ባሉት ሥርዓቶች በትምህርት መስክ የስልጤ ህዝብ ተጠቃሚ እንዳልነበር ያመለከቱት አቶ ሳኒ ባለፉት ሰባት ዓመታት ዞኑ ከክልሉ ትምህርት ቢሮና ከተለያዩ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ጋር ባደረገው ርብርብ ከ20 በመቶ የማይበልጠውን የ1ኛ ደረጃ ጥቅል የትምህርት ተሳትፎ በአሁኑ ወቅት መቶ በመቶ ማዳረስ መቻሉን ተናግረዋል።

ቀደም ሲል የስልጤ ህዝብ ከፍተኛ የሆነ የጤና ችግር ይደርስበት እንደነበርና በተለይ የእናቶችና ህፃናት ሞት ጎልቶ ይታይ እንደነበር አስታውሰው በአሁኑ ወቅት የዞኑ ህዝብና አስተዳደሩ ባደረጉት ርብርብ በየአካባቢው 188 የጤና ኬላዎችንና 12የጤና ጣቢያዎችን በመገንባት ህዝቡ መሰረታዊ የጤና አገልግሎትን እንዲያገኝ የሚያስችሉ ተግባራት መከናወናቸውን ተናግረዋል።

በተጨማሪም በዞኑ በሚገኙ በሁሉም የገጠር ቀበሌዎች ከ570 በላይ የጤና ኤክስቴንሽን ባለሙያዎችን በመመደብ ህብረተሰቡ ጤናውንን አስቀድሞ መከላከል የሚችልበትን ስርዓት በማመቻቸት ጤናማ የአኗኗር ዘይቤን እንዲከተል በመደረግ ላይ መሆኑን ተናግረዋል።

በምጣኔ ሐብት በኩልም ዞኑ ለግብርናና ለኢንቨስትመንት ካለው ምቹ ሁኔታ በመነሳት አብዛኛው አርሶአደር በባሕላዊና ዘመናዊ መስኖ ልማት በመታገዝ በዓመት ሁለት ጊዜ በማምረት የምግብ ዋስትናውን በማረጋገጥ ላይ እንደሚገኝና በከተማ አካባቢም በሚካሄዱት የኢንቨስትመንት ሥራዎች በርካታ ህዝብ ተጠቃሚ እየሆነ መምጣቱን ተናግረዋል።

በመሠረተ ልማት ዝርጋታ በኩልም ሁሉም የዞኑ ወረዳዎች የስልክ፣የመብራት፣የትራንስፖርትና መሠል አገልግሎቶች የተሟሉላቸው ሲሆን በቀበሌ ደረጃ ሙሉ በሙሉ ለማዳረስ አስተዳደሩ ጥረት እያደረገ መሆኑንም አቶ ሳኒ አስታውቀዋል።

በዞኑ በተካሄደው የሚሊኒየሙ የግል ድርጅቶች፣ባለሃብቶችና ነጋዴዎች እንዲሁም የወጣቶች ፌስቲቫል ላይ ከ1ሺህ በላይ የሚሆኑ የወረዳና የዞን አመራሮች እንዲሁም ባለሃብቶች የተገኙ ሲሆን የዞኑን የኢንቨስትመንት አማራጮች የሚያመላክት የፓናል ውይይት መደረጉን ዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል ዘግቧል።