ቢሮው የአርብቶ አደሮችን ህይወት ለመለወጥ በመሰረተ ልማት አግልግሎቶች ትኩረት እንደሚሰጥ ገለፀ

ጅጅጋ መስከረም 25/1999/ዋኢማ/ የሶማሌ ክልል አርብቶ አደሮች ልማት ማስተባበሪያ ቢሮ የአርብቶ አደሮችን ህይወት ለመለወጥ የሚያስችሉ የመሰረተ ልማት አገልግሎቶችን ለማሟላት ቅድሚያ ትኩረት መስጠቱን ገለፀ።

የቢሮው ተወካይ አቶ አብዲ ቢሌ ለዋልታ አንፎርሜሽን ማዕከል እንደገለፁት ቀደም ሲል በተናጣል ሲካሄዱ የነበሩና የአርብቶ አደሮችን ህይወት ለመለወጥ ግንባር ቀደም ሚና ያላቸው የጤና፣ የንፁህ መጠጥ ውሃና የትምህርት አገልግሎቶች እንዲሁም የግብርና ኤክስቴንሽን ድጋፎች በተያዘው የበጀት ዓመት በተሻለ ሁኔታ ለማከናወን ታቅዷል።

የመሰረተ ልማት አገልግሎቶቹ በመስኖ በሚለሙ ቦታዎች ለሚሠፍሩና እንደየምርጫቸው ተንቀሳቅሰው መኖር ለሚፈልጉ አርብቶ አደሮች ትኩረት በመስጠት የሚከናወን ሲሆን ስራዎቹን ለማሳካት የጤና ኤክስቴንሽን፣ የአማራጭ መሠረታዊ ትምህርት አመቻቾችና የልማት ጣቢያ ሠራተኞች ስልጠና በስፋት እየተሰጠ መሆኑን ተናግረዋል።

ቢሮው ከአርብቶ አደር ልማት ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ካላቸው አሥር የመንግስት መስሪያ ቤቶችጋር የሚካሄዱ የልማት ሥራዎች የሚቀናጁበት ዕቅድና መመሪያ መዘጋጀቱን የጠቀሱት ተወካዩ በክልሉ የሚከሰተውን የምግብ ዋስትና ችግር ለማቃለል ባለፈው ዓመት የተጀመረው የመስኖ ልማትን የማስፋፋትና የእንስሳት ሃብት ገበያን የማመቻቸት ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።

በተለይም የእርሻ ስራን ለሚጀምሩ አርብቶ አደሮች መሠረታዊ አገልግሎቶቹን ከማቅረብ ጎን ለጎን የሙያ ድጋፍ፣ የግብኣትና የአዳዲስ ቴክኖሎጂዎች አቅርቦት እንደሚደረግ ከተወካዩ ገለፀፃ ለመረዳት ተችሏል ሲል ዋልታ ዘግቧል።