|
ብሔራዊ ቡድኑ ከናሚቢያ ጋር ላለበት ጨዋታ የፊታችን ሐሙስ ወደ ዊንድሆክ ሊጓዛ ነው |
| አዲስ አበባ መስከረም 23/1999/ዋኢማ/ በ2008 በጋና በሚካሄደው 26ኛ የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ለመሳተፍ የማጣሪያ ጨዋታዎች በማድረግ ላይ የሚገኘው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የፊታችን ዕሁድ ከናሚቢያ ጋር ላለበት ጨዋታ በቂ ዝግጅት ማድረጉን አሰልጣኝ ስዩም አባተ ገለፁ። ቡድኑ የፊታችን ሐሙስ ወደ ዊንድሆክ ይጓዛል። አሰልጣኝ ስዩም ዛሬ ለዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል እንደገለፁት፤ ቡድኑ በራሱ ሜዳ ከሊቢያ ጋር ባደረገው ጨዋታ የተስተዋሉበትን ድክመቶች አርሞ በኳስ ላይ የተመሰረተ ልምምድ ሲያደርግ ቆይቷል። በአሁኑ ሰዓት ቡድኑ 20 ተጫዋቾችን ያካተተ መሆኑን ገልፀው፤ ከታዳጊ ብሄራዊ ቡድኑ አንድ በረኛ፣ አንድ ተከላካይና ከሊቢያ ጋር በተደረገው ጨዋታ በቡድኑ ያልተካተተው ደብሮም ሐጎስ መካተቱን ገልፀዋል። "የናሚቢያ ብሔራዊ ቡድን በአጨዋወት ስልቱም ሆነ በሰውነት አቋሙ ከኛ ብዙ የማይራራቅና በተመሳሳይ አቋም የምንገኝ ቢሆንም ፈጣንና በአጭር የኳስ ቅብበል ላይ የተመሰረተ ጨዋታ በመጫወት ቡድናችን የተሻለ በመሆኑ በአሁኑ ጨዋታ አሸንፈን አሊያም ውጤት አስጠብቀን እንወጣለን" ብለዋል - አሰልጣኝ ስዩም። የቡድኑን አምበል ሙሉአለም ረጋሳ "በሀገር ውስጥ ብቻ ማሸነፍ ለታለመው ግብ ስለማያደርሰን ከሀገር ውጪ ባለው ጨዋታ አሸንፈን ወይም አቻ ወጥተን ወደ ፊት መጓዝ እንፈልጋለን" ብሏል። በሊቢያ ጨዋታ ወቅት የሜዳው ጭቃማ መሆን አስቸጋሪ እንደነበረ ያስታወሰው የቡድኑ አባል ሰብስቤ ሸገሬ በበኩሉ "አሁን በደረቅ ሜዳ ስለምንጫወት የተሻለ ውጤት ለማምጣት እንጫወታለን" ማለቱን ዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል ዘግቧል። |
|
|
|
|