|
የሀረሪን ክልል የጤናሽፋን ወደ 92 በመቶ ለማሳደግ ጥረት እየተደረገ ነው |
| ሐረር መጋቢት 12 /1998/ዋኢማ/ በሐረሪ ህዝብ ክልል ባለፈው ዓመት 76 ነጥብ 4 በመቶ የደረሰውን የጤና ሽፋን ዘንድሮ ወደ 92 በመቶ ለማሳደግ ከመንግስት በተመደበ 5 ነጥብ 5 ሚሊየን ብር ወጪ የ12 የጤና ፕሮጀክቶች ግንባታ በመካሔድ ላይ መሆኑን የክልሉ ጤና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ምክትል ኃላፊ ዶክተር ብርና አብዶሽ ዛሬ ለዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል እንደገለጹት፤ የጤና ፕሮጀክቶቹ ግንባታ በመካሔድ ላይ የሚገኙት በክልሉ የገጠርና የከተማ ቀበሌዎች ውስጥ ነው። የክልሉን የጤና ሽፋን ለማሳደግ በክልሉ ጤና ቢሮ አማካኝነት ካለፈው ህዳር ወር ጀምሮ በመካሔድ ላይ ከሚገኙት ከእነዚሁ ፕሮጀክቶች መካከል 5ቱ አዲስ ሲሆኑ ቀሪዎቹ ነባር ፕሮጀክቶች መሆናቸውን ዶክተር ብርና ገልጸዋል። ከሚከናወኑት የጤና ፕሮጀክቶች መካከልም የ5 ጤና ኬላዎችና የሁለት ሆስፒታሎችን የክፍል ጥበት ለማቃለልና የአገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል የሚያስችሉ ተግባራት እንደሚገኙበትም ዶክተር ብርና ገልጸዋል።
እንዲሁም የሐረር ነርሶች ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት የመማሪያ ክፍሎች፣ የተማሪዎች ማደሪያ ህንጻ፣የሳንባ ነቀርሳና የምስራቅ አርበኞች ሆስፒታል ተጨማሪ ግንባታዎች እንዲሁም የውስጥ ለውስጥ መንገድና የአስፋልት ጥገና ሥራዎች እንደሚከናወኑም አብራርተዋል። ከዚህም ሌላ የጀነሬተርና የአርተፊሻል መተንፈሻ መሳሪያ ግዥ ፣የጤናና የስነ ምግብ እንዲሁም የአካባቢ ንጽህና አጠባበቅ ስራዎች ፣የቆሻሻ ማጠራቀሚያና ማቃጠያ ግንባታና ሌሎችም እንደሚገኙበትም ገልጸዋል። በሌላ በኩል ከ2 ሚሊየን ብር በሚበልጥ ወጪ በሐረር ከተማ በተለምዶ 4ኛ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ የተጀመረው የጤና ጣቢያ ግንባታ ሙሉ በመሉ መጠናቀቁን ጠቁመው ከሥራው ተቋራጭ ድርጅት ጋር ርክክብ እንደተፈጸመ ሥራ እንደሚጀመርና ከ25ሺ ለሚበልጡ ሰዎች አገልግሎት እንደሚሰጥ ተናግረዋል። የሁሉም ጤና ተቋማት ግንባታ በመጪው ሰኔ ወር ሙሉ በሙሉ ሲጠናቀቅ ባለፈው ዓመት 76ነጥብ 4 በመቶ የደረሰው የክልሉ የጤና ሽፋን ወደ 92 በመቶ ከፍ እንደሚልና ህብረተሰቡም በየአቅራቢያው የተሻለ የጤና አገልግሎት ተጠቃሚ እንደሚሆን የቢሮው ምክትል ሀላፊ አስረድተዋል። በመገንባት ላይ ያሉት ቀሪዎቹ የጤና ኬላዎችም ከ50 በመቶ እስከ 85 በመቶ የግንባታ ደረጃ ላይ እንደሚገኙ ጠቁመው፤ በመጪው ሰኔ ወር ተጠናቀው ለአገልግሎት ሲበቁ ከ20 ሺ በላይ ለሆኑ ሰዎች አገልግሎት እንደሚሰጡ አስረድተዋል። ቢሮው በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ከመንግስት በተመደበ 5ሚሊዮን ብር ወጪ የ13 ፕሮጀክቶችን ግንባታ አጠናቆ ለአገልግሎት ማብቃቱንም ከቢሮው ምክትል ሀላፊ የተገኘው መረጃ ያመለክታል። |
|
|
|
|